ሰሞኑን “Ethiopia” በተሰኘውና ከ50 ሺህ በላይ ተከታዮች ባሉት የቲክቶክ ገፅ ላይ “በአዲስ አበባ ቦሌ አካባቢ ከባድ የመኪና አደጋ እና የእሳት ቃጠሎ ደረሰ” የሚል አስደንጋጭ ቪዲዮ ተለቆ ተመልክተናል።
ይህ መረጃ የሰዎችን ትኩረት እና ስጋት በእጅጉ የሳበ ሲሆን፣ ትርታ ቼክ መረጃውን እስካጠናከረበት ሰዓት ድረስ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከ418 ሺህ በላይ እይታዎችን ማስተናገድ የቻለ ሲሆን ከ4,800 በላይ Likes እና ከ1,500 በላይ Shares ተደርጎ በስፋት ሲሰራጭ ቆይቷል።
https://vt.tiktok.com/ZSxFFJKN5/

ትርታ ቼክ የተሰራጨውን በቪዲዮው ላይ የሚታዩትን የአካባቢ ገፅታዎች በጥንቃቄ መርምሯል። ለዚህም InVid WeVerify የተሰኘውን የቪዲዮ ማጣሪያ ዲጂታል መሳሪያ እና የነገሮች መፈለጊያ ቴክኖሎጂዎችን ተጠቅሟል።
በተደረገው ጥልቅ የቴክኖሎጂ ማጣራት እና የእይታ ምልከታ መሰረት በቪዲዮው ላይ የሚታዩት የመንገድ መሠረተ ልማቶች፣ የህንፃዎች አወቃቀር፣ የትራፊክ ምልክቶች እና አጠቃላይ የአካባቢው ገፅታ ፈፅሞ ከአዲስ አበባ ከተማ በተለይም ከቦሌ አካባቢ ጋር ምንም ዓይነት ግንኙነት የሌለው መሆኑን አረጋግጠናል።
ቪዲዮው በሌላ ሀገር የተከሰተን የቆየ አደጋ በማህበራዊ ሚዲያ እይታን (Views) ለማግኘት ሲባል ብቻ “ቦሌ ላይ የተከሰተ አደጋ” ተደርጎ በሀሰት የተጋራ ነውና መረጃውን ትርታ ቼክ ሀሰተኛ ሲል በይኖታል ።